>

Sunday, 28 September 2014

መስቀልና ደመራ ክፍል÷ ፩

                           ክፍል አንድ
እግዚአብሔር የሠራቸው ታላላቅ ሥራዎችን ስንመለከት በምልክት የተገለጡ ናቸው፤ የሙሴ መስፍንነት፣ የአሮን ሊቀ ካሕንነት የተረጋገጠው በአሮን በትር ምልክትነት ነው፤ አብርሃም ልጁ ይስሐቅን ሊሰዋ በታዘዘ ጊዜ የሞርያ ተራራን እንዲመርጥ የተደረገው እግዚአብሔር በተራራው ላይ ካሳየው የብርሃን ምልክት የተነሣ ነው በእርግጥ እሱም ራሱ ለሌላ ምሥጢር ምልክት እንደ ነበረ ምንም ጥርጥር የሌለው ጉዳይ ነው፤ እርሱ ይስሐቅ ሊመጣ ላለው ለወልደ እግዚአብሔር አምሳል ምልክት ነበርና፡፡ ድንግል ማርያም እና ቅዱስ መስቀልንም ለመዳናችን ምልክት አድርገን የተቀበልናቸው ሲሆን ከዚህ አስቀድሞ ለእነርሱም የተቀመጠ ምልክት ነበራቸው፤የአሮንን ክብር ያስመለሰች በትረ አሮን፣ ድንቅ አድራጊዋ በትረ ሙሴ፣ የይስሐቅ ቤዛ የሚሆን በጉን ያስገኘች ዕፀ ሳቤቅ የእመቤታችን እና የቅዱስ መስቀል ምልክቶች ነበሩ፤ ምልክቶቹ ምልክት እየተሰጣቸው ትውልዱን ከተስፋ መቁረጥ ታድገውታል የመዳን ምልክቶችን በሕዝቡ መካከል እንዲገለጡ ማድረጉም በዋናነት ለሕዝቡ ተስፋ እንዲሆኑ ነው፤ እንዳሁኑ ዘመን መያዣ ያልተሰጠው በሩቅ በሚሰማው ተስፋ ብቻ የሚኖር ባለ ተስፋ ትውልድ ነበርና፤ አሁን ሥጋውና ደሙን መያዣ አድርጎ ሰጥቶናል የተስፋይቱን ምድር ከሰላዮች ድምጽ ሰምተን ሳይሆን በዐይናችን አይተን አረጋግጠናል ነገር ግን እስክንወርሳት ብቻ ‹‹ትምጻዕ መንግሥትከ ›› ስንል እንኖራለን መንግሥተ ሰማያት ይሏችኋል ሌላ እንዳይመስላችሁ ክርስቶስ ራሱ ነው መንግሥተ ሰማያት የተባለው፡፡