>

Wednesday, 16 September 2015

የመ ንቃት ዘመ ን



የሰው ልጆች አባት አዳም ከተፈጠረ በስምንተኛው ቀን ላይ ከባድ እንቅልፍ ውስጥ እንደነበረ በታላቁ የእግዚአብሔር መጽሐፍ ውስጥ ተጽፎ እናነባለን፤ በተፈጠረ ማግስት የነበረውን ታላቁን ሰንበት ካከበረ በኋላ እንዲሠራ የታዘዘውን ሠርቶ ሲጨርስ አዳም ብቻውን እንዳይሆን የፈለገው አምላክ ‹‹ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም …›› በማለት ብቻውን ዓለምን እንደ ማይሠራት አስቦ የምትረዳውን ሔዋንን በከባድ እንቅልፍ ውስጥ ሳለ ፈጠረለት፡፡ እንቅልፍ ምሳሌው የሆነ ሞትን የምታመጣ ሔዋን በከባድ እንቅልፍ ውስጥ ከነበረው አዳም ጎን እንዲህ ባለ ሁኔታ ውስጥ ተፈጠረች፡፡ የእንቅልፍን ታሪክ ያወቅነው ከዚህ ጀምሮ መሆኑ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ለባሕርያችን የሚስማማ ሆኖ እንድናርፍ በተሰጠን ሌሊት ውስጥ እንቅልፍን ከዚህ ክፉ ዓለም ወጥተን ሌሎች በልባችን ያሰብናቸውንም ሆነ ያላሰብናቸውን የምናይበት አንዳንድ ጊዜም ያላወቅነውን የምናውቅበት ሌላ ጊዜም ወደ ፊት በሕይወታችን ውስጥ ሊሆን በእግዚአብሔር የታሰበልንን ከመሆኑ አስቀድሞ የምናይበት ነው፡፡
    እግዚአብሔር ሥራው ግሩም ነውና የምንወደውን ብርሃን ወስዶ በጨለማ ያሳርፈናል፤ እያየን እየሰማን ሊያደርግ ያልፈለገውን ነገር በእንቅልፍ ውስጥ ሳለን ያደርግልናል፤ በሌላ አነጋገር ሌሊት ቀን የምንሠራውን የምናቅድበት እንቅልፍም የሕይወታችንን መስመር የምናይበት የሕይወታችን አንድ ጠቃሚ ክፍል ነው ማለት ነው፤ የቀደሙት አባቶቻችን ታላቁን የክርስቶስን ሰው የመሆኑን ነገር ያዩት በሦስት መንገድ ነው፡-
§  በራእይ
§  በሕልም
§  ግልጥ ሆኖ ከእግዚአብሔር በሚመጣ መልእክት ነው
ያለ እንቅልፍ ሕልም የለም፤ ያዕቆብ በፍኖተ ሎዛ ባያንቀላፋ ኖሮ ከምድር እስከ ሰማይ በተዘረጋው መሰላል ላይ የተቀመጠውን ንጉሥ እንዴት ማየት ይችል ነበር፤ ‹‹ዛቲ ይእቲ ሆኅታ ለሰማይ ዝዬ ይትሐነጽ ቤተ እግዚአብሔር፤ ይህች የሰማይ ደጅ ናት በዚህ ስፍራ የእግዚአብሔር ቤት ይሠራል›› ብሎ መናገርን እንዴት ሊያገኝ ይችላል፤ በእንቅልፉ ውስጥ ያዕቆብ ወደ ፊት የሚሆነውን አይቶ ተናገረ ከአርባ ስምንቱ የአይሁድ ምኩራባት አንዱ እሱ በተኛባት ስፍራ በቤቴል እንደሚሠራ መሰከረ፤ ነቢይነቱ ከእንቅልፍ በኋላ ተጀመረ፤

Wednesday, 2 September 2015

እግዚአብሔር ለምን ይናገራል?


በእግዚአብሔር ዘንድ ያለው ቃል በእኛ ዘንድ ካለው ቃል የተለየ ቃል ነው፡፡ ከእኛ ልዩ የሚያደርገው ምንድነው ካላችሁኝ በእርሱ ዘንድ ያለው ቃል ዓለም የተፈጠረበት ቃል እንጅ እንደ እኛ የተፈጠረ አይደለም፤ ዮሐ 1÷3 የእኛ ቃል አካል የሌለው ዝርው ሲሆን የእርሱ ቃል ግን ከልብ ከእስትንፋስ የተለየ ሦስተኛ የሥላሴ አካል ነው፤ በእኛ ዘንድ ያለው ቃል ስም የሌለው ሲሆን በእርሱ ዘንድ ያለው ቃል ግን በተለየ ስሙ ወልድ ተብሎ የሚጠራ አካላዊ ስም አለው፤ የእኛ ቃል ያልነበረበት ጊዜ ያለውና ኋላም በሞት የሚወሰን ሆኖ ሳለ የእርሱ ቃል ግን አርምሞና ጽርዓት የሌለበት ነው፡፡ እኛ ምናውቀው ዓለም ከተፈጠረችበት ጊዜ ጀምሮ ያለውን ዘመን ነውና ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እግዚአብሔር ሰሚ ከተገኘ ሳያቋርጥ ይናገራል፡፡ 
ግን እግዚአብሔር ለምን ይናገራል?
1. ሌሊቱ እንዲነጋ፡-

 ይህች ዓለም በጨለማ ተጀምራ በጨለማ የምታበቃ ክፉ ዓለም እንደሆነች የታመነ ነው፡፡ በተፈጠረችበት በዚያ በመጀመሪያው ቀን የነበራት ሌሊት አብረዋት በእለቱ የተገኙትንና ከባዶነት የገላገሏትን ብርሃናውያን ፍጥረታትን መላእክትን ጭንቀት ውስጥ ያስገባ አስጨናቂ ለሊት ነበር፤ መላእክት ከብርሃን መፈጠራቸው የከበባቸውን ጨለማ ሊያርቅላቸው አልችል ብሎ በከበባቸው ጨለማ ከተማቸው ተሸበረ፤ ጨለማው ሌላ ጨለማ ፈጠረባቸውና ዲያብሎስ ልንገሥባችሁ አለ፤ ብቻ ያ ጨለማ መዘዙ ብዙ ነበር፡፡ በዚህ ሁሉ ጭንቀት ውስጥ ለነበሩ መላእክት ሰምተውት የማያውቁት የእግዚአብሔር ድምጽ ካልሆነ ሌላ ከዚህ ሁሉ ሊገላግላቸው የሚችል ምን ሊኖር ይችላል፡፡ በእርግጥም ይህ ሁሉ ችግርና ጭንቅ ነገር እግዚአብሔር እስኪናገር ድረስ ነበርና እግዚአብሔር ሲናገር ሁሉም ተስተካከለ፡፡

ዓለም እንድትስተካከል አሁንም
የእግዚአብሔር ድምጽ አስፈላጊ ነው፡፡ ያስጨነቀን ሌሊት እንዲነጋ ሽብር የፈጠረብን ነገር እንዲረጋጋ በዙሪያችን ካሉት ጋር አንድ ልሳን እንድንነጋገር እግዚአብሔር ሊናገር ግድ ነው፡፡ እግዚአብሔር እስኪናገር እኮ ነው መላእክት ከአራት ተከፍለው አንዱ ክፍል እንጦርጦስ ሁለተኛው ክፍል በዐየር ሦስተኛው በዚህ ምድር ዐራተኛውም በሰማይ ተነጣጥለው የቀሩት እግዚአብሔር ካልተናገረ በባልና በሚስት በወንድምና በእህት በአባትና በልጅ በአማትና በምራት በጎረቤትና በጎረቤት መካከል አንድነት እንዴት ሊኖር ይችላል፤ መተማመን ይጠፋል አንድነት ፀሐይ እንደነካው ጉም ይሆናል ፍቅር እንደ ጤዛ ፈጥኖ ይረግፋል ውበት እንደ ቅጠል ይጠወልጋል እግዚአብሔር ካልተናገረ ሁሉም ከንቱ ይሆናል፡፡