>

Thursday, 29 October 2015

ማደሪያውን አይቸዋለሁ

በብሉይ ኪዳን ከነቢያት አንዱ ለእግዚአብሔር ሲሳል ‹‹ኢይሁቦን ንዋመ ለአእይንትየ ወኢድቃሰ ለቀራንብትየ፤ ለዐይኖቸ እንቅልፍን ለቅንድቦቼም ሽልብታን አልሰጣቸውም›› ብሎ የእግዚአብሔርን ማደሪያ እስኪያይ ድረስ ለሰውነቱ እረፍትን እንደማይሰጥ በልቡ ጽኑ መሀላን ምሎ እንደ ነበረ ተመዝግቧል መዝ 131÷2፤ እንደ ተናገረውም ‹‹ናሁ ሰማዕናሁ በኤፍራታ ወረከብናሁ ውስተ ዖመ ገዳም፤ እነሆ በኤፍራታ በዱር ተጥሎ እንደ ኅጻናት ሲያለቅስ ሰማነው ከእንግዲህስ ወዲህ ወደ እግዚአብሔር ማደሪያዎች እንገባለን›› ብሎ የእግዚአብሔርን ማደሪያ አግኝቶ እስኪመለስ ድረስ ሱባዔውን አላቋረጠም::

 በሐዲስ ኪዳንም እንደዚሁ ‹‹ሊቅ አይቴ ተሐድር›› እያሉ ከሀገር ወደ ሀገር እየተዘዋወረ ያስተምር የነበረውን ጌታ በኋላው እየተከተሉ ማደሪያውን እስኪያሳያቸው ድረስ ይጠይቁት የነበሩ ሁለት ሰዎች እንደነበሩ ተጽፏል፡፡ ዮሐ1÷39 እርሱም ያልፈለጉትን የሰው ልጆች ሊፈልግ ነውና የመጣው የሚፈልጉትን ሰዎች ኑ ማደሪያዬን አሳያችኋለሁ ብሎ እስከ አሥር ሰዓት ድረስ ከእርሱ ጋር ውለው ማደሪያውን አይተው እንዲመለሱ አድርጓቸዋል፡፡

ለቅዱሳን የእግዚአብሔርን ማደሪያ ከማየት ሌላ ደስታን የሚፈጥርላቸው ምን ነገር አለ? ማደሪያውን ፍለጋ ባሕር ያቋርጣሉ፣ በዋሻ ውስጥ መንገድ ያበጃሉ፣ ዓለም የማትገባቸው በመሆኗ የፍየል ሌጦ የበግ ለምድ ለብሰው በዋሻ በፍርኩታ ሰዎች ሆነው ሳለ ከሰው ተለይተው ይኖራሉ፣ መንገዳቸውን ከዓለም ለይተው ወደ እግዚአብሔር ይጓዛሉ፡፡

ዛሬ ለብዙ ዘመናት የተመኘሁት ተሳክቶልኝ እኔም የእግዚአብሔርን ማደሪያ ለማየት በጣና ባሕር ጀርባ ላይ እየተጓዝሁ ነው፤ የተጫንሁበት ጀልባ ወደፊት እየተጓዘ እኔ ግን በፍኖተ አእምሮ ወደ ኋላየ ተመልሼ የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 8÷23 አንድም እያልሁ እየተረጎምሁ በገሊላ ባሕር ላይ በመርከብ ብዙ ጊዜ ይመላለሱ የነበሩ ደቀ መዛሙርቱን አስታወስሁ፤ኅሊናዬ በገሊላ ባሕር እንጅ በጣና ላይ የሚጓዝ አልመስለኝ አለ። መዳረሻዬም የጥብርያዶስ ማዶ ጌታ ተዓምራት ያደርግበት የነበረው ሥፍራ የገሊላ መንደር ይመስለኝ ነበር፡፡ ከመርከብ ስወርድ የጴጥሮስን አማት በንዳድ ታማ ጌታ ሲፈውሳት እንደማገኛት እያሰብሁ ነው የምጓዘው፡፡ እንዲያውም ባይገርማችሁ በአካል ሳይሆን በኅሊናዬ ተነሣሁና ጌታዬን  እንደ ሐዋርያት ከመርከቡ ጀርባ ፈለግሁት በሥጋ ሕግ ተኝቶ የማገኘውና ዓለም እንዲህ በጭንቀት ማዕበል ስትጠፋ ቤተ ክርስቲያን በትምህርተ መናፍቃን ስትዳፈን አይገድህምን? ልለው ፈለግሁ ውስጤን ፍርሃት ተሰማው፤ ያን ጊዜ በዘለዓለማዊ እንቅልፍ ውስጥ የነበርን እኛን ሊያነቃን ተኝቷል እንጅ ለባሕርዩ እንቅልፍ የሚስማማው ይመስልሃልን?ብሎ የሚገሥጸኝ መላኩን የላከብኝ መስለኝ፡፡

Monday, 19 October 2015

ነገረ ቤተ ክርስቲያን-- ክፍል ስድስት


አሥሩ የማሕሌት ደረጃዎች

( ከባለፈው የቀጠለ……)
6.   ቁም
በቤተ ክርስቲያናችን ቁም ንባብ፣ ቁም ዜማ ቁም ጸናጽል ያለ ሲሆን ሁሉም ትርጉማቸው ተመሳሳይ ነው፤አሁን ግን የምናየው ቁም ጸናጽልን ነው፡፡ በንዋያተ ቅድሳት ክፍል የምናየው ስሆነ ነው እንጅ ጸናጽ በራሱ የክርስቶስን መከራ የአበውን ተስፋ ፍጻሜ የሚያሳይ ነው- አሠራሩ፡፡ በጸናጽል ከምናቀርባቸው አንልግሎቶች አንዱ ይህ የቁም ጸናጽል ሁለት ነገሮችን የሚያሳይ ነው

6.1   የመጨረሻዋን ቀን ለማስታወስ:-

በእግዚአብሔር  ፊት የምንቆምባት የመጨረሻቱ የፍርድ ቀን በሁችንም ሕይወት የምትታወስ ቀን ናት ኃጥአንም ሆነ ጻድቃን የማትቀር በመሆኗ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹እስመ ሀለወነ ኩነ ንቁም ቅድመ ምኩናኑ ለክርስቶስ ሁላችንም በክርስቶስ ፊት እንቆም ዘንድ አለንና›› እያለ ያችን ቀን ያስታውሳታል፡፡ ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ስዚች ቀን ሲናገር ከምፈራቸው ሦስት ቀኖች አንዷ ናት ብሏታል፤እንኳን በፈጣሪ ፊት መቆም በንጉሥ ፊት መቆም እንኳን ምንኛ ያስፈራል፡፡ ይህች ቀን ግን የመጨረሻውን ፍርድ መስማት በቅድመ እግዚአብሔር የምንቆምባት ሰዓት ስለሆነች የምታስፈራ እንላታለን፡፡
ታዲያ ሊቃውንቱ ያንጊዜ ማረን ራራልን ለማለት ዛሬ እንደነቢዩ ዳዊት ‹‹በጽባሕ እቀውም ቅድሜከ ወአስተርኢ ለከ፤ በማለዳ በፊትህ ቆሜ እታይልሀለሁ›› መዝ 63  እያሉ በቁም ጸናጽል ፈጣሪያቸው ፊት ቆመው ፈጣሪያቸውን ያመሰግናሉ፤ ምንጊዜም ቢሆን ማኅታውያኑ በእጃቸው በጨበጡት ጸናጽል ቁም ዜማውን እየጸነጸሉ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹እስመ ሀወነ ኩልነ ንቁም ቅድመ ምኩናኑ ለክርስቶስ›› እያሉ ማሰብ ይገባቸዋል

6.2 ክርስቶስ በዐውደ ፍትሕ መቆሙን ለማስታዎስ፡-

ከቤተ መንግሥት እስከ ቤተ ክህነት የተሸሙ ሹማምንት ሁሉ ፍርድ እንዲሰጡ ተጠይቀው በአንድ ወንጀለኛ ላይ ተስማምተው የፈረዱበት ጊዜ በታሪክ ከዚህ ቀን በስተቀር ይገኛል ብየ አላስብም፤
ከነም እንኳን በቅዱስ ጳውሎስ ላይ እንደተደረገው በወንጀለኛው ላይ ይግባኝ ተጠይቆበት የሆነ እንደሆነ ነው፡፡ የዛሬው ግን ከዚህ ሁሉ የተለየ ነው፤ የሹመት ዘመኑን የጨረሰው ሀና በዚያው ዘመን ባለሥልጣን የነበረው ቀያፋ ሌሊቱን ሙሉ ሲያዩት ካደሩ በኋላ ሲነጋ ደግሞ ወደ ቤተ መንግሥት ሹማምት ነገሩ ተመልሶ ከጲላጦስ ወደ ሔሮድስ እየተመላለሰ የክስ ሂደቱ ሲታይ አረፈደ፤ በእርግጥ በእግዚአብሔር ዘንድ የታሰበው ክርስቶስ የሚሞትባት ቀትረ ዐርብ እስክትደርስ እንጅ ፍርዱ እንደማይቀየር በእርሱ ዘንድ የታወቀ ስለሆነ ዝም ብሎ ፍርዱን ተቀበለ፡፡
      ፍርዱን ከሰውልጆች ያስወግድ ዘንድ በፍርድ ዐደባባይ ቆሞ ፍርድ ተቀበለ፤ ‹‹አዳም ሆይ ቀድሞ መሬት ነህ ወደ መሬትነትህ ትመለሳለህ……..›› በፈራጁ ላይ ካልፈረዱበት ፍርዱ ከሰው ልጆች እንዴት ሊወገድ ይችላል፡፡ ኢሳ 53÷6 በነገር ሁሉ የተፈረረደበትንአዳምን መስሎ በመምጣቱ ሰራዊተ መላእክት በፊቱ ቆመው ማገልገል የማይቻላችው የሰራዊት ጌታ በዳኞች ፊት ቆሞ የሞት ፍርዱን ሰማ፡፡