>

Wednesday, 18 November 2015

ሦስቱ ስደታት

   ክፍል ሁለት
ባለፈው ክፍል እንደተመለከትነው በኃጢአቱ ምክንያት ርስቱን ተነጥቆ ስፍራውን ለቆ የመጣው የሰው ልጅ በዚህም ዓለም በልዩ ልዩ መንገድ ከአንዱ ወደ አንዱ ሲዘዋወር ይኖራል፡፡ ከሀገሩ ወጥቶ ከሄደ ደግሞ በልዩ ልዩ ፀዋትዎ መከራ መፈተኑ የማይቀር ጉዳይ ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ስደትን ከባድ እሚያደርገው ልጅ ይዞ የሚያደርጉት ስደት ነው ልጅ ይዞ አስከትሎ የሚያደርጓት ስደት የመከራዎች ሁሉ እናት ናት፡፡ በእመቤታችን ም የሆነው ይህ ነውና በመከራ የሚተካከላት ማንም የለም፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ እንደ ተናገረው ‹‹ሐዊረ ፍኖት በእግሩ ሶበ ይስዕን ሕጻንኪ ያንቀዐዱ ኀቤኪ ወይበኪ በእግሩ መሐድን በደከመ ጊዜ ወደ አንች ቀናብሎ ያለቅሳል›› እንዳለ በነገር ሁሉ ሕጻናትን መስሏልና ሕጻናት እናቶቻቸውን የሚጠይቁትን ሁሉ ጠይቋታል፡፡ በነፍስሽ ሰይፍ ያልፋል ተብላ ነበርና በብርቱ ፈተና ውስጥ አለፈች፡፡
ሔሮድስ ግን እሷን አሰድዶ እንደ ሊባኖስ ዝግባ ክብሩ ከፍ ከፍ አለ፤ የሊባኖስ ዝግባ የትኛውንስ ያክል ቢገዝፍ በቅርንጫፉ ዓለምን ቢከድን የሰማይ አዕዋፍ ቢንጠላጠሉበት፣ የምድርም እንስሳት ቢጠለሉበት ምን ቁም ነገር አለው፤ አንዲት ክብሪት እንዳልነበረ ታደርገው የለ! ይገርማል እኮ! ያ ግዙፍ ዛፍ በትንሽ ክብሪት በትንሽ ምሳር የሚጠቃ ይመስላችኋል? አንዲት ክብሪት ብዙ ደን ታጠፋለች፤ የሔሮድስም ግነት እግዚአብሔር ቁጣውን እስኪገልጥ ብቻ ነው፡፡
      እግዚአብሔር ሦስት ዓመት ከመንፈቅ የንስሐ ጊዜ ቢሰጠው አልመለስ ያለ ሔሮድስን ከስሩ ነቅሎ እንዳልነበረ አድርጎ በሞት ቀጣው፤ ያንጊዜ ‹‹ኃጥዕ እንደ ሊባኖስ ዝግባ ገኖ አየሁት ስመለስ ግን አጣሁት ቦታውን ፈለግሁ አላገኘሁትም›› መዝ 36÷35-36 ብሎ ነቢዩ ዳዊት የተናገረው ደረሰ፡፡ ቀናት ሲቆጠሩ ለካ ኃጢአቱም በእግዚአብሔር ፊት እየተቆጠረበት ነበርና የዘመኑ ሳይሆን የክፋቱ ቁጥር ሲሞላ ይግባኝ የሌለው ፍርድ ተፈረደበት፤ ዘመን ባይሞላም ክፋት ሲሞላ ያለ ጊዜም ሊያስነሣ ይችላል ክፉ ሰው እስከ ዕድሜው ፍጻሜ የሚኖር አይደለም፤ እንዲያው ኃጢአቱ ሲሞላ እግዚአብሔር ከተወሰነለት ዕድሜ በታች ሊያነሣው ይችላል እንጅ፡፡
በቅዱስ ሉቃስ ወንጌል የተመዘገበችው በለስ እንደ ሔሮድስ ያሉ ሰዎችን ትመስላለች፤ የእርሻው ባለቤት ለሦስተኛ ጊዜ መጥቶ አንዳች ፍሬ ያላገኘባት በዚህም ምክንያት ‹‹እንግዲህስ ምድራችንን እንዳታቦዝን ቆርጠህ ጣላት›› የተባለላት፡፡ ሉቃ 13÷6 ሔሮድስንም ጠበቀው እና በጎ ፍሬ ማፍራት አልችል ሲል አጫጆችን ልኮ አጨደው፡፡

ሦስቱ ስደታት

  
               ክፍል አንድ

በዚህ ምድር ላይ በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ እመቤታችን የከበረ ማንም የለም፤ ክብሯ ከምድራውያኑ ጋር ብቻ ሳይሆን ከሰማውያኑ ጋር ስንኳን ሊነጻጸር የማይችል ታላቅ ነው፤ ነገር ግን በዚህ ምድር እንደ እመቤታችን በመከራ የተፈተነ ደግሞ ማንም የለም፤ እንደ ሚታወቀው ይህች ዓለም ለእግዚአብሔር ሰዎች የፈተና መድረክ እንጅ የስጦታ ሰገነት አይደለችምና በነገር ሁሉ እንደ ሰማዕታት ተፈትናለች፡፡ ከልጅነቷ እስከ እለተ ሞቷ፣ ከቤተ መቅደስ እስከ ቤተ ዮሐንስ ሁሉም ያለፈችባቸው መንገዶች በእሾኽ የታጠሩ እንጅ የአበባ ምንጣፍ የተጎዘጎዘባቸው አልነበሩም፡፡
      በዚህ ሁሉ ፈተና በእመቤታችን ሕይወት ውስጥ አስቸጋሪው የፈተና ወቅት ያለፈው ጌታችን በተወለደ ማግስት በተነሣው ስደት ነው፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡- ጌታችን የመጣው ዓለምን እንደ ሰውነቱ ዞሮ ሊባርካት እንደ አምላክነቱም ሕይወትን ሊሰጣት ነውና ሰይጣን በክፉ ሀሳቡ ያረከሳትን ዓለም ለመቀደስ ኃጢአት ወደ በዛባቸውና በጣዖት በኃጢአት የተሰነካከሉትን ለማዳን ሰይጣን ሳያውቅ ባስነሣቸው ክፉ ሰዎች ምክንያት ክርስቶስ ከገሊላ ወደ ግብፅ እንዲሰደድ ግድ ሆነ፡፡ ከመካከለኛው ምሥራቅ በረከት ወደ ምድረ አፍሪቃ ተሸጋገረች፡፡
      የገሊላ ንጉሥና ሕዝብ ሳያውቁት በረከታቸውን ለሌላ ሕዝብ አሳልፈው ሰጡ፤ በነቢይ ‹‹ሕዝቤ ዕውቀት ከማጣቱነ የተነሣ ጠፍቷል›› እንደ ተባለ የልደት እለት እነሱ ተኝተው ሳሉ በዚያች ሌሊት ከሩቅ ምሥራቅ የመጣው ሕዝብ በረከተ ልደቱን ተሳትፎ ተመለሰ፤ ዛሬ ደግሞ  እግዚአብሔር ኢየሩሳሌምን ከአህጉር ሁሉ መርጦ በመካካላቸው ቢወለድ ለተመረጡለት በረከት ብቁ ባለመሆናቸው በረከታቸውን እያሳደዱ መርገማቸውን አጨዱ፡፡ እጃችን ላይ ያሉ ግን ሳንጠቀምባቸው የሚያልፉ በረከቶች እንዳይኖሩ መጠንቀቅ ያስፈልገናል፡፡ ገሊላውያን በወቅቱ የነበራቸው ሀሳብ ከሀገር ሲያስወጡት ከሰውም ልብ የሚያስወጡት መስሏቸው ነበር፤ ውስጠ ምሥጢሩ ግን ፈቃደ እግዚአብሔር ነበረበት፤ ያኔ ጌታ እንዲሰደድ ባይሆን ኖሮ ታላላቁን የግብፅ ገዳማት እነ ገዳመ አስቄጥስን፣ ገዳመ ሲሀትን  በሀገራችንም እነ ዋልድባን፣ ጣና ቂርቆስን ማግኘት ባልተቻለም ነበር፡፡ ይህን እግዚአብሔር እንጅ ሌላ ማን ሊያውቀው  ይችላል?
      በዚህ ወቅት ታዲያ የንጉሡ እናት የሰውና የመላዕክት እመቤት ድንግል ማርያም የደረሰባትን ፈተና ቆጥሮ መጨረስ አይቻልም፤ አባቷ አዳም እናቷም ሔዋን የደረሰባቸው መከራ በሥጋም በነፍስም ከባድ ነበርና ለዚያ ማስረጃ እንዲሆን እመቤታችን ያለ ርህራሄ አስቸጋሪ የሚባሉ ፈተናዎችን አሳልፋለች የሰማዕታት እናታቸው ናትና በምትቀበለው መከራ ለሰማዕታት መንገድ ጠራጊ አደረጋት፡፡ እመ ብዙኃን የሚያሰኛትም አንዱ ይህ ነው እመ ብዙኃን የምትባለው ስለሦስት ነገር ነው:-

እመ መናንያን

እመ ሐዋርያት

እመ ሰማእታት በመሆኗ ነው።
የመናንያን እናት የምንላት በሦስት ዓመት እድሜዋ ወገኖቿን የአባቷንም ቤት ረስታ በቤተ መቅደስ ስለኖረች ነው አባቷ ዳዊት እንደተናገረ መዝ 44 ከቤተ መቅደስ በአስራ ሁለት ዐመቷ እንድትወጣ የተደረገ ቢሆንም እንኳን ወደ ወገኗቿ ለመሄድ አላሰበችም ንጉሡ እግዚአብሔር ውበቷን የወደደላት መናኒተ ዓለም ናትና፡፡