መጻጉዕ
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ
በማዕከለ ምድር ቀራንዮ ተሰቅሎ ዓለምን ከማዳኑ አስቀድሞ በለመለመ ሳር ትምህርቱ በጠራ ውኃ ተዓምራቱ ሰዎችን እየፈወሰ የባሕርይ
አምላክነቱን በሥራው እያስመሰከረ ምድርን ዞረ፤ በተለይም የባሕርይ ልጅነቱን ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ካስመሰከረ በኋላ በገዳመ ቆሮንቶስ
ድል የነሳውን ሰይጣን በከተሞችም እያሳደደው ማዳኑን ቀጠለ፤ በዚህ ሰዓት ከፈወሳቸው ሕሙማን መካከል እንደ መጻጉዕ ደዌ የፀናበት
ሰው በቅዱስ ወንጌል አልተመዘገበልንም፤ ይህ ሰው እንደ ሌሎቹ በሽተኞች ከባለመድኃኒቶች ዘንድ ስለመሄዱ አልተነገረለትም፣ የጉባኤው
ቦታ በሰዎች በመጨናነቁ ምክንያት መግቢያ እንኳን ቢያጡ ጣራውን አንሥተው ወደ ክርስቶስ ፊት የሚያቀርቡ ወዳጆችም አልነበሩትም እሱ
እራሱ እንደገለጠው ሰው ባጠገቡ አልነበረምና ዮሐ 5፥5
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕሙማን
የእግዚአብሔርን ምሕረት ደጅ በሚጠኑባት ቤተ ሳይዳ ተገኘ፤ ቤተ ሳይዳ አምስት መመላለሻ የነበራት የሕሙማን ስፍራ ናት፤ ታመው ይመጡባታል
እንጅ ታመው የማይመለሱባት፤ እየተጨነቁ መጥተው እየተደሰቱ የሚመለሱባት፤ በልመና ገብተው በምስጋና የሚመለሱባት፤ የእግዚአብሔር
ፍቅር የሚገለጥባት ናት- ቤተ ሳይዳ፡፡ በዚህ ስፍራ የሚድኑ የእግዚአብሔር መልአክ ወርዶ ውኃውን በባረከው ጊዜ ቀድሞ የሚገባ አንድ
ድውይ ብቻ ነው የሚድነው፤ ለመዳን ጥቂት ጉልበት እና የሚያግዝ ሰው ያለው ቀድሞ ይፈወስ ነበር፤
ዮሐንስ ወንጌላዊ ግብሩን እንጅ ስሙን ያልገለጠው ሕሙም ለብዙ ቀናት በዚህ
የምሕረት ስፍራ ተኝቶ ቆይቷል ሌሎቹ እየተፈወሱ ሲመለሱ እያየ ከነደዌው ዘመናትን አስቆጠረ፤ ቀድሞ እንዳይገባ ጉልበቱን ደዌ አድቅቆታል፤
ከታመመ ሠላሳ ስምንት ዓመቱ ነውና መዳን እያማረው ሳይድን ዘገየ፡፡
በዚህ ሁኔታ ሳለ ነው ኢየሱስ ክርስቶስ
የመጣው፤ እስኪያነጋረው ድረስ አዳኙ እንደመጣለት አላወቀም፤ ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ብሎ ሲጠይቀውም ለመዳን የሚያበቃውን ሁኔታ
እንዲያመቻችለት ይመስላል እስካሁን ያልዳነበትን ምክንያት እየዘረዘረ መዳን የሚፈልግ መሆኑን አስረዳ፤ ምን ያድርግ ብዙ ሕዝብ ይከተለው
ነበርና ከነዚህ አንዱን ቢያዝዝልኝ አንሥቶ ወደ ባሕሩ ያስገባኝ እና እድናለሁ አለበለዚያም ደግሞ ጎልማሳ ነውና አንስቶ ወደ መጠመቂያው
ያደርሰኛል ብሎ ጎመጀ እንጅ ድምፁን ሰምቶ የሚያድነው እርሱ እንደሆነ ማወቅ አልቻለም፡፡ እርሱ ግን መን እንደሚፈልግ ካረጋገጠ
በኋላ ‹‹ተነሥተህ አልጋህን ተሸክመህ ሂድ›› አለው በቅጽበትም ተረፈ ደዌ ሳይኖርበት ተነሥቶ አልጋውን ተሸክሞ ወጣ፡፡
ይህ ሰው የሁላችንም አባት አዳም
ነው፤ ወንጌላዊው ግብሩን እንጅ ስሙን ያልጠራው ለምን ይመስላችኋል? ደዌ የፀናበት አዳማዊ ሕይወትን የሚወክል ስለሆነ ነው፡፡ የመጠመቂያው
ስፍራ ጵሩጳጥቄ (የመዋኛ ስፍራ) የተባለችው ኦሪት ናት፤ አምስት መመላለሻ ነበራት ማለት አምስት ክፍል ሁና መሠራቷን ያስረዳል
1. ዘፍጥረት 4. ዘኁልቁ
2. ዘፀአት 5.
ዘዳግም ናቸው፡፡
3. ዘሌዋውያን
እነዚህ አምስቱ ሕግጋት አምስት
የመሥዋዕት ዓይነቶች ነበሯቸው፤
1. የሚቃጠል መሥዋዕት 4. የበደል መሥዋዕት
2. የደኅንነት መሥዋዕት 5. የእህል ቁርባን የሚባሉት ናቸው፡፡
3. የኃጢአት ማሥተስረያ መሥዋዕት
በዚህ ሁሉ ሥርዓቷ ሕጓ አንዱን
አዳምን ማዳን አለመቻሏን ተመልከቱልኝ፡፡ ነገር ግን በውኃው ዳር ለተቀመጡ በሽተኞች አንዳንድ ሰው ይፈወስ እንደነበረ መነገሩ በኦሪት
ፍፁም መዳን ባይሰጥም በመልእክተኞች የሚደረግ ጥቂት ጥቂት የእግዚአብሔር ምሕረት ይታይ ነበር መካኖች ወልደዋ፣ ሕዝቡ ከባርነት
ቤት ወጥቷል፣ ባሕር ተከፍሏል፣ ከነዘር እባብ መርዝ ድኗል እንዲህ የመሳሰሉ ትንንሽ ተዓምራቶች አለመከልከላቸውን መናገር ነው ነገር
ግን የአዳምን ባሕርይ መፈወስ ሳይችሉ ቀሩ፡፡ ካህና በሹመታቸው በሚያቀርቡት መሥዋዕታቸው ነቢያቱ በሚፀልዩት ጸሎታቸው አዳምን ማስታረቅ
አልቻሉም ለዚህ ነው መጻጉዕ - አዳም ‹‹ሰው የለኝም›› ብሎ የተናገረው
እውነቱን ነው! ተስፋ ያደረጋቸው ጻድቃን ልጆቹ ባሕርዩን ከመርገም አላዳኑለትም ሁሉንም ሞት ገዛቸው እንጅ ሮሜ 5 ለአዳም ሰው
ቢኖረው ኖሮ እግዚአብሔር ለምን ሰው ሆነ? እግዚአብሔርም እንደ ቀድሞው በመልአክ ሊያድነው አልፈለገም እራሱ ሰው ሁኖ ወደ እርሱ
በሥጋ መጣ፡፡
ይገርማል! አምስት እርከኖች ወደነበሯት
የመጠመቂያ ስፍራ መጣ የታመመውን ሰውም ቀርቦ ‹‹ልትድን ትወዳለህን›› ብሎ ጠየቀው መባሉ ለምን ይመስልሃል? አባታችን አዳም ዕፀ
በለስን በበላ ጊዜ አምስቱም ኅዋሳቱ በድለዋል፤ በዚህ ሰዓት እግዚአብሔር የኃጢአት ደዌ ወደ ፀናበት አዳም መጥቶ ‹‹አይቴ ሀሎከ አዳም›› ማለቱ እና ዛሬ በመጻጉዕ ታሪክ ላይ ‹‹ልትድን ትወዳለህን?››
ብሎ የጠየቀው ጥያቄ ተነጻጻሪ ነው፤ ሁለቱም ሰውን ለማዳን ካለው ጥልቅ ፍላጎት የተነሣ ነው፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ሰውን የሚያድነው
ለመዳን ያለውን ፍላጎት አይቶ እንጅ ሁሉን ቻይነቱ የሰውን ፈቃድ አትከለክልበትም ሰው ባለ አዕምሮ ፍጡር ነውና ሞትንም ሆነ ሕይወትን
የመምረጥ ዕድል ተሰጥቶታል፡፡ ቀርቦ ጠየቀው ማለት ባሕርዩን ዝቅ አድርጎ ሰውን በባሕርይ መሰለው ማለት ነው፤ መጻጉዕ የሚያድነውን
ጌታ አለማወቁ ስለምን ነው ቢሉ ለጊዜው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው በሆነ ጊዜ ከሰዎች እንዳንዱ ሆኖ በእለተ ዐርብ ተሰቅሎ እስኪያድነን
ድረስ አይሁድ ዕሩቅ ብዕሲ ወልደ ዮሴፍ (ሎቱ ስብሐት) ሲሉት የነበሩ መሆናቸውን ለመግለጽ ነው፡፡
በፈወሰውም ጊዜ ፈውሱ ከባለ መድኃኒቶች
ልዩ ነው ብለናል ምክንያቱም ባለ መድኃኒቶች የፈወሱት ሰው በዕለቱ ተነሥቶ አልጋውን ተሸክሞ የሚያስኬድ ዐቅም አያገኝም በዚያውም
ላይ ባለመ ድኃኒቶች የጠጣበትን ጽዋዕ የተኛበትን አልጋ የእኛ ይገባል እያሉ ያስቸግራሉ እሱ ግን እንዲህ አይደለም፤ አልጋህን ተሸክመህ
ሂድ አለው እንጅ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምን እስኪያድነው ድረስ ብዙ ዘመናትን በደዌ ሥጋ በደዌ ነፍስ እንደተያዘ መቆየቱ
ግልጽ ነው ነገር ግን በእለተ ዐርብ አንድ ጊዜ ባቀረበው መሥዋዕት ፈጥኖ የአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ነፍሳትን ወደ መዳን
ጠራቸው እንጅ ከማዳን አልዘገየም አንድ ጊዜ ተወለደ፣ አንድ ጊዜ ሞተ፣ አንድ ጊዜ ወደ ሲኦል ወረደ ለዘለዓለም ነፍሳትን ሁሉ ወደ
ገነት መለሰ የሰውን ባሕርይ ወደ የማነ እግዚአብሔር አሳረገ፡፡
መጻጉዕ መዳኑን ሳያዩ በሰንበት
ስለመዳኑ ይካሰሱ የነበሩ አይሁድ እንደነበሩ ሁሉ በአዳም መዳንም የተቃወሙ አጋንንት ነበሩ፡፡
መልካም የመዳን ሳንምንት