>

Friday, 23 August 2019


ዜና ፍልሰታ ፪
እንዲህ ነበር፡-
ከገነት ወደ ምድር የተደረገውን ስደት፣ ከምድር ወደ ሰማይ የሚደረገውን ደግሞ ፍልሰት እንለዋለን፡፡ የእስራኤል ከግብጽ መውጣት ፍልሰት ሲሆን የአሕዛብ ከተስፋይቱ ምድር ከኢያሪኮ መውጣት ግን ስደት ነው፡፡ ዛሬ ቅድስት ድንግል እመቤታችን ከሚያረጀው ዓለም ወደ ማያረጀው ዓለም የፈለሰችበትን ቀን እናስታውሳለን፡፡
አባቶቻን ሐዋርያት በገቡት ሱባኤ መሠረት የእመቤታንን በድነ ሥጋዋን መልአከ እግዚአብሔር አምጥቶ ሰጥቷቸው በጌቴሴማኒ ቀብረዋታል የእናትና የአባቷ እንዲሁም የጠባቂዋ የቅዱስ ዮሴፍ መቃብርም በዚሁ ስፍራ ይገኛል፡፡ ሱባኤ የገቡበት የጸለዩበት ጉዳይ ሥጋዋን አግኝተው እንደ ልጇ መቃብር መቃብሯን መሳለም ነበር እንጅ ትንሣኤዋን ማየት ስላልነበረ - የሱባኤው ዓላማ ፤ ቀብረዋት ወደየሀገረ ስብከታቸው ተበታትነዋል፡፡
ቶማስ ከመቃብሯ ላይ አልተገኘም ነበርና ከሀገረ ስብከቱ ወደ ኢየሩሳሌም በደመና ሲመለስ እሷን መላእክት ሲያሳርጓት በዐየር አግኝቷታል፡፡ የእግዚአብሔር ምሥጢሩን ተመልከቱት! ሐዋርያት ሱባኤ የገቡት ለመቃብሯ እንጅ ለትንሣኤዋ ስላልነበረ ትንሣኤዋን አላሳያቸውም፤ ነገር ግን የእመቤታች ትንሣኤ ከቤተ ክርስቲያን ተደብቆ እንዳይቀር በቶማስ በኩል እንዲገለጥ አደረገው፡፡ እኛስ ሐዋርያት ያላስተማሩንን ምን ብለን ተነሣች ዐረገች እያልን እናስተምር ነበር፤ እግዚአብሔር የልጇን ትንሣኤ ዘግይቶ ያመነውን ቶማስን የእሷን ትንሣኤ ቀድሞ እንዲያምን አደረገው፡፡
ቶማስ መጥቶ በነገራቸው መሠረት ትንሣኤዋን ለማየት ለሁለተኛ ጊዜ በዓመቱ ሱባኤ ገቡ እንደ ቀድሞው በሁለተኛው ሱባኤ መጨረሻ ላይ ትንሣኤዋን አልገለጠላቸውም አሥራ አራተኛውን ቀን አሳልፎ በአሥራ ስድስተኛው ቀን ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ እመቤታችንን አስከትሎ በሐዋርያት መካከል ተገልጦ አሳያቸው፡፡
ነሐሴ አሥራ አራት ተቀብራ የተነሣቸውም በዚያው ቀን ነሐሴ አሥራ አራት ዕለቱም እሑድ ነው ነገር ግን ዛሬ እኛ ትንሣኤዋን የምናከብረው በነሐሴ አሥራ ስድስት ነው ለሐዋርያት የተገለጠበት ቀን ነውና፡፡ በሌላ መንገድ ሐዋርያት ማለት ቤተ ክርስቲያን ናትና ቤተ ክርስቲያን ትንሣኤዋን ባየችበት ቀን ነው እያከበርን ያለነው ማለት ነው፡፡
እመቤታችን በተነሣችበት እለት ነሐሴ አሥራ አራት በእለተ እሑድ ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ በገነት ያለውን ምሥጢር ያሳያት ዘንድ ወሰዳት፤ በገነት ውስጥ መዐዛቸው ልብን የሚመስጥ ዕፀዋትን አየች፤ ጌታችንም ከሁሉም የሚበልጥ መዓዛ ያለው ርሔ ከሚባለው የሽቱ ዛፍ ቆርጦ ሰጣት፡፡ በዚያም የንፁሐን ደናግልን የቅዱሳንን ሁሉ ማደሪያ አየች፤ ዳግመኛ የሰማዕታትን ማረፊያና የተሰጣቸውንም ክብር ታይ ዘንድ ሰማዕታት ወዳሉበት ስፍራ ወሰዳት፤ አይታም አደነቀች፡፡
ከዚህም በኋላ ‹‹ዕርጊ ውስተ ሰማይ ከመ ትርአዪ ምሥጢረ በህየ፤ በሰማይ ያለውን ምሥጢር ትመለከች ዘንድ ወደ ሰማይ ውጭ አላት›› በዚያም የእግዚአብሔር የሀብቱን መዛግብት ተመለከተች፤ የበረዱን፣ የዝናሙን ፣የቁርን፣ የጠልን፣ የውኃውን የእሳቱን፣ የነፋሱን መዛግብት ተመለከተች ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስም በብርሃን ሠረገላ ተቀምጦ ይታይ ነበር፡፡
ኤልያስ ሔኖክ ቆመው የሚጸልዩበትን ስፍራ በመጀመሪያው ሰማይ ላይ ተመለከተች፡፡ በሁለተኛውና በሦስተኛው ሰማይ መላእክት ክንፎቻቸውን ዘርግተው በማያቋርጥ ቅዳሴ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ሲሉ ሰማቻቸው፡፡
በዐራተኛው ሰማይ እንደ እንቊ የሚያበራ በአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ስም የተሰየመ አሥራ ሁለት በር ያለው አዳራሽ ተመለከተች፤ በእያንዳንዱ በር አሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ቁመው ምስጋና ሲያቀርቡ ከኋላቸውም 12ቱ ሊቃነ መላእክት በየበሮቹ ቁመውበታል ፡፡ በኢየሩሳሌም ሰማያዊት በታላቁ በር በኩልም አብርሃም፣ ይስሐቅ፣ ያዕቆብ፣ ዳዊት ቆመው ለንጉሠ ሰማይ ወምድር ምስጋና ሲያቀርቡ አየቻቸው፡፡
ወደ ውስጥም በገባች ጊዜ ከመጀመሪያው በር ላይ ስትደርስ ነገደ መላእክት ሰገዱላት፤ ከሁለተኛው በር ስትደርስ ሱራፌል አመሰገኗት፤ ከሦስተኛው በር ኪሩቤል ዘመሩላት፤ ከአራተኛው በር ስትገባ ሥልጣናት፣ ከአምስተኛው ሊቃናት፣ ከስድስተኛው ሚካኤልና ገብርኤል ሰገዱላት፤ ከሰባተኛው በር ሠራዊተ መላእክት ጩኸው ሲያመሰግኑ ሰማች፡፡ ከስምንተኛውም ከዘጠነኛውም ከአሥረኛውም ከአሥራ አንደኛውም ከአሥራ ሁለተኛውም በር ገባች ፍጥረታት ሁሉ ዝናም፣ መብረቅ፣ ነፋስ፣ ፀሐይ ጨረቃ ከዋክብት አመሰገኗት፡፡ በዚያ የነበሩ መላእክት ሁሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡
የእመቤታችን ወደ ሰማይ የገባችው መግባት እንዲህ ነበረ፡፡ በኋላም ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የሚመሰገንበትን ጽርሐ አርያምን አሳያት አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ የሚመሰገኑትን ምስጋናም ሰማች፡፡  የእመቤታችን የምድር ላይ የመከራ ጊዜ አብቅቶ ወደ ዘለዓለማዊው ተድላ ደስታ የፈለሰቸው እንዲህ ነበር፡፡
ይቅርታ! በበዓሉ ዕለት እንዲለቀቅ ታስቦ የተዘጋጀ ቢሆንም internet ወደሚገኝበት ስፍራ ለመሄድ ጊዜ በማጣቴ የዘገየ ነው፡፡


Saturday, 17 August 2019


ዜና ፍልሰታ
ከመጽሐፈ ልደታ የተቀዳ ታሪክ ነው
ፈላስያን ከሀገር ወደ ሀገር ይዘዋት የሚሰደዱ ስንቃቸው፣ አዳም ከገነት በተሰደደ ጊዜ በልቡ ትክሻ የተሸከማት ተስፋው ዛሬ ከሚያልፈው ወደማያልፈው ከሚያረጀው ወደ ማያረጀው ሄደች፡፡
ከመሞቷ አስቀድሞ ከሄዋን ጀምሮ ያሉ ቅዱሳት አንስት መጥተው እጅ ነሷት፤ እናቷ ሐና፣ ከዘመዶቿ ወገን የምትሆን ኤልሳቤጥም መምጣታቸውን ቅዱስ ጴጥሮስ ተናግሯል፡፡ እነሱ መጥተው ሰላምታ እያቀረቡላት ሳሉ ከአዳም ጀምሮ ያሉ አበው እጅ ሊነሷት ሲመጡ ማየቱንም ቅዱስ ጴጥሮስ መስክሯል፡፡ ሁሉም አበው እጇን እግሯን እየሳሙ ተሳለሟት አብርሃም፣ ይስሐቅ፣ ያዕቆብ ሁሉም ከጻድቃን ወገን የቀረ አልነበረም፡፡
ዳዊት በሚዘምረው መዝሙር ቤቱ በጣዕመ ዝማሬ ተሞላ፤ ልጇ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አሥራ ሁለቱ ሊቃነ መላእክት የወርቅ ጥና ይዘው እንዲወርዱ አዘዘ፤ ንፁሕ ዕጣን እያገቡ እመቤታን ታማ የተኛችበትን አልጋ እየዞሩ ሲያጥኑ አካባቢውን በጎ መዓዛ አወደው፤ ከእነርሱም ጋራ አባቶቿ ነቢያት ማዕጠንት ይዘው ይታዩ ነበር፡፡ ከገነት እፀዋት አበቦችን ይዘው የመጡ መላእክትም ነበሩ
ለዚህ ክብር የበቁባት ልጃቸው ወደ ሰማይ የምትወሰድበት ጊዜው አሁን ነውና ከአበው ማንም በሰማይ የቀረ የለም፤ ምድሩን ሰማይ፣ ሰማዩን ምድር ያደረገችው በእመቤታችን ዕለተ ዕረፍት ማን በሰማይ ይቀራል፡፡ ከመወለዷ አስቀድሞ በትንቢት ደጅ ይጠኗት እንደነበረ ዛሬም ነፍሷን ይዞ ልጇ በሚያሳርጋት ጊዜ እያመሰገኑ ሊቀበሏት ይጠባበቃሉ፡፡
በዐፀደ ነፍስ ካሉ ቅዱሳን ጀምሮ በዐፀደ ሥጋ እስካሉ ሐዋርያት ድረስ ከበዋት እንደቆሙ ልጇ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ ወረደ፤ ከአጠገቧም ቆሞ ሰላምታን ከሰጣት በኋላ ነፍሷን ከሥጋዋ ለይቶ ተቀበላት፡፡
 ነፍስን የነሳላት ነፍሷን በእቅፉ አድርጎ ሳማት፤ ያቀፈችው ጌታ አቀፋት፤ የሳመችው ልጇ ሳማት፤ በዙሪያዋ የነበሩ ቅዱሳን ሁሉ ደስ አላቸው፤ መላእክትም አመሰገኑ፤  ነቢዩ ዳዊት ‹‹ወትቀውም ንግሥት በየማንከ በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኁብርት፤ ንግሥቲቱ የወርቅ ልብስ ለብሳ በቀኝህ ትቆማለች›› የሚለውን መዝሙሩን ሲዘምር ቅዱሳን ሁሉ አብረውት አመሰገኑ፡፡ በቅዱሳን ዘንድ ነፍስ ወደ ፈጣሪዋ ስትመለስ የሚሰማው ምስጋና እጅግ ታላቅ ነው በዚህ ዓለም መወለዳችን ምጥ የሚያስረሳ ደስታን ያመጣል በወዲያኘውም ዓለም መንግሥተ ሰማያትን መውረሳችን በዓለም የደረሰብንን መከራ ሁሉ የሚያስረሳ ደስታን ስለ ሚያመጣ ቅዱሳን ሁሉ እልልታን ያሰማሉ እመቤታችንም ነፍሷ ከሥጋዋ ስትወጣ እልልታው የደመቀ ነበረ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ዐይኖቿን ከደናቸው ጴጥሮስና ጳውሎስ ደግሞ እጆቿን እግሮቿን አስተካከሉ፡፡ የለበሰችውን ልብሷን ግን ማውለቅ አልቻሉም፤ በሰማያዊ ብርሃን ሰውነቷ ተሞልቷልና ከዚያ በኋላ ልብሷን መንካት አልቻሉም፡፡ ይህ ታሪክ ጥር 21 የተፈጸመ ነው የእመቤታችንም ፍልሰት ያንጊዜ ነው፡፡  የሰሞኑን ታሪክ ደግሞ በቀጣይ እንመጣበታለን ፡፡

Saturday, 10 August 2019


በፍልሰታ እንፍለስ
ይህ ጾም ጾመ ማርያም ወይም ጾመ ፍልሰታ ለማርያም ተብሎ ይጠራል፤ በዚህ ጾም እመቤታችንን, አባቶቻችን ቅዱሳን ሐዋርያትን እናስታውስበታለን እነዚያ መከረኞች የጌታ ሐዋርያት በምድር ላይ ያለዉን መከራ ሁሉ ቀምሰውታል፤ ከክርስቶስ ዕርገት በኋላ ምሥጢር የሚጠይቁት መከራቸውን የሚረሱት፣ ከድካም የሚያርፉት ወደ እመቤታችን  ቅድስት ማርያም ዘንድ እየሄዱ ነው፡፡ ከየሀገረ ስብከታቸው ወደ ኢየሩሳሌም በደመና ተጭነው መጥተው ኀይል መንፈሳዊ በረከት ሰማያዊ ከእሷ ተቀብለው ይመለሳሉ መለኮትን በዳሰሱ እጆቿ ትዳስሳቸዋለች፤ ከሰባቱ የእሳት መጋረጃ ውስጥ ያለውን የመለኮት ምሥጢር ባዩ ዐይኖቿ ታያቸዋለች ቁስላቸው ድኖ ስብራታቸው ተጠግኖ ወደ መንበራቸው ይመለሳሉ፡፡
አሁን ግን ነገሩ እንደዛ አይደለም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በአፀደ ሥጋ ከእነርሱ ከተለየች ከቤተ ዮሐንስ ከወጣች ወራት ተቆጥረዋል፤
ያውም የድካም ጊዜ ምርኩዛቸውን እመቤታችንን ቀብረው መቃብሯን አለማወቃቸው ልባቸውን በኃዘን የሚሰብር ሆኖባቸዋል በዚህ ምክንያት ነው ሱባኤ በነሐሴ አንድ ቀን ጀምረው የገቡት፡፡
§  ሱባኤው በድነ ሥጋዋን ለማግኘት ነበር ነገር ግን ያልጠበቁትን ትንሣኤዋን አሳያቸው፡፡
አግኝተው ይቀብሯት ዘንድ በመሻት ሱባኤ ገቡ እግዚአብሔር ጥቂት ሲሹ ብዙ መስጠት ልማዱ ነውና አግኝተው እንዲቀብሯት ሳይሆን አግኝተው ወደ ሰማይ ስታርግ እንዲያይዋት ፈቀደላቸው፤
§  ነፍስ የተለየውን ሥጋዋን ብቻ ሳይሆን ነፍስ ከሥጋዋ ተዋሕደው እንዲያይዋት ዳግመኛ ቀርበው ከእጇ እንዲባረኩ አደረጋቸው፤
v  ለዚህ ሁሉ ምክንያቱ ከፍልሰታ አስቀድመው መፍለሳቸው ነበር ሰውነታቸውን በጾም ከመብል ከመጠጥ፣ ደስታቸውን በኃዘን፣ ዕረፍታቸውን በትጋት፣ ሳቃቸውን በለቅሶ፣ እንቅልፋቸውን በአገልግሎት አፈለሱት ይህን ዓለም እረሱት እሷ ከእነርሱ ስትወሰድ እነሱም ያለ ጊዜአቸው ይህን ዓለም ጥለውት ተሰደዱ፤ ወንጌል ሲሰብኩ ይውላሉ ሌሊቱን እንቅልፍ በማጣት በትጋሓ ሌሊት  ያድራሉ፡፡
እግዚአብሔር የልባቸውን መሻት እስኪያደርግላቸው ድረስ እስከ መንበረ ፀባኦት ድረስ እየገሰገሱ ደጅ ጠኑ፡፡ አስቀድመው ፈልሰው ፍልሰቷን ተመለከቱ፡፡
v  እስኪ እኛም እግዚአብሔር ይረዳን ዘንድ በፍልሰታ እንፍለስ፤ በዚህ ወራት ኃዘን እና ለቅሶ ጸሎትና ምኅላ ጎን ለጎን የሚሠራ ሥራ አይደለም፤ ቤተ ክርስቲያን ወገቧን ታጥቃ ልትሠራው የሚገባ ዋና ተግባሯ ነው፤ ጠላት ሳያፈልሰን እኛ በፍልሰታ እንፍለስ አብያተ መቃድሳቶቻችን በእሳት የተተኮሱብን፣ መምህራኑ ወምበራቸውን እያጠፉ ወደ ከተማ የፈለሱብን፣ ምዕመናኑ ማተባቸውን የበጠሱብን ካህናት በአለባበሳቸው በአኗኗራቸው ቅጥ ያጡብን፣ ጳጳሳቱ እውነትን መድፈር አቅቷቸው አፍረው የተመለሱብን እኛ የዚህ ዘመን ክርስቲያኖች ነን፡፡
ግብረ ክርስትናውን ትተነው ስንፈልስ እነሱ ደግሞ በዚያው ገቡና ቤተ ክርስቲያኒቱ ከሀገር ትፍለስ አወ! ድሮ አገር ነበረች አሁን ግን ትፍረስ፤
አወ! ድሮ ንጉሥ ንግሥት ነበረች አሁን ግን ጵጵስናዋም ይርከስ፤
 አወ! ድሮ የሕግ መምህር ነበረች አሁን ግን ያለ ሕግ ትወቀስ! ትከሰስ! እያሉ ዘበቱባት፡፡ እጃቸውን ይዛ ለጣቶቻቸው ጥበብን፣ ጽሕፈትን፣ ድጉሰትን ያስተማረቻቸው ኢትዮጵያውያኑ እራሳቸው እጃውን አወጡባት፡፡ ለአንደበታቸው ፊደልን ቋንቋን ያስጠናቻቸው አንደበታቸውን ከፈቱባት፡፡ በቀረጸችው ፊደል ዜና ሞቷን ጻፉላት፡፡ አያችሁት እኛ አስቀድመን ከትምህርተ ክርስትና መፍለሳችን ቤተ ክርስቲያንችንን አፈለሳት፤ አሁንም እላችኋለሁ በፍልሰታዋ እንፍለስ፡፡ ያንጊዜ አጋንንት ከሀገራችን ይፈልሳሉ፤ ጠቢባን ጥበብን ይናገራሉ ሰነፎቹ ዝም ይላሉ፤ ኢትዮጵያ ዐዋቂዎች የሚናገሩባት አርዮስፋጎስ ትሆናለች፡፡

እግዚአብሔር ከረዳኝ ዜና ፍልሰታን ጾሙ ሳያበቃ አንድ ቀን እጽፍላችኋለሁ

Friday, 2 August 2019



ሐሽማል፤ ሐሽማል፤ ሐሽማል
  ስሙን ስሰማ በቁሜ ፈዘዝሁ፡፡ መጽሐፉን ገልጬ ሳነበው ትንሽ ተሻለኝ፡፡ ሐሽማል  በማዕበል ፈጠነ የተዘጋጀ መጽሐፍ ሲሆን በሀገራዊ ጥበብ ላይ ያጠነጥናል፡፡ የጠቢባኑንና የባለቅኔዎችን  በደመና የመጫን ጥበብ በአቡሻክር ቀመር ቀምሮ ቁጭ ያደርጋል፡፡ ከዚህ በፊት በደመና የሚሄዱ ጠቢባን መኖራቸውን ሲሰሙ አንዳንዶቹ በአስማት ሊሆን ይችላል ብለው እንደሚያስቡ አልጠራጠርም እኔም ቢሆን ጥልቀት ያለው ዕውቀት በዚህ ዘርፍ ስላልነበረኝ ዕፁብ ዕፁብ ብዬ አልፈው ነበር፡፡ የሐሽማል ደራሲ ማዕበል ፈጠነ ግን በአስማት ሳይሆን በአቡሻክር ቀመር ነው ሲል የውስጤን ጥርጣሬ አውጥቶ ጥሎ አቡሻክሩን ቀምሮ አሳየኝ፡፡ እናም ለጥበብ ልቤን ሰጠሁ፡፡ ከዚህ ዐልፎ የጠቢቡ ሖረን በጥበብ የሕይወትን ውኃ ፍለጋ የሊቅ ዐፅቁን በድቅድቅ ጨለማ ቀይ ብርሃን የሚተፋ መጽሐፍ አምጥቶ አስደመመኝ፡፡ በተለይ በጎንጅ ደብረ ጥበብ ተዋነይ በጥበቡ የሰወራትን ውኃ ለጠጣ ሰው  ቅኔ መዝረፍ ቀላል እንደሆነ ከአፈ ታሪክ አልፎ አማናዊ መሆኑን ሊያሳምነኝ ዳዳው፡፡
 ‹‹በእርግጥ ጥበብ ኅብረ ብዙ እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ ለጥበብ  እንደ ኪሩቤል አይኖቿ ብዙ ናቸው፡፡ እንደ ሱራፌልም መላ አካሏ በክንፍ የተሞላ ነው፡፡ ወደ ወደደችውም ትበራለች፡፡ የምታርፍበትን ካገኘች በልቡ ላይ ታርፋለች፡፡ ሰባት ምሰሶዋችን አቁማ ቤቷን ሠርታ ወዳጆቿን ሁሉ ወደ ቤቷ ትጠራለች፡፡ ማዕዱ ከቀረበ በኋላ ራሷ የወይን ጠጅ ሆና ብቅ ትላለች፡፡ ሲጠጧት ከወይን ይልቅ ትበረታለች፡፡ጠቢባንን ታሰክራለች፡፡ ለዚህም ምስክሬ ራሱ የመጽሐፉ ደረሲ ማዕበል ፈጠነ ነው፡፡ መምህር ማዕበል ፈጠነ ጥበብ ካሰከረቻቸው ወጣት ባለ ቅኔዎች ዋናው ሲሆን በቅኔው ዘረፋ ጊዜ የምር ሊወድቅ ሲንገዳገድ ብዙ ቀን ዐይቻለሁ፡፡ ዛሬ ደግሞ ሐሽማል የሚባል መጽሐፍ ጽፎ እኔንም አስክሮኛል፡፡ እናንተም ከጥበቡ ተቋደሱ፡፡