>

Saturday, 28 September 2019


መስቀል በኢትዮጵያ
እግዚአብሔር ለሕሙማን የሚቀባውን ዐጽቀ በለስ በኢትዮጵያ እጅ እንዳስቀመጠው መጽሐፍ ቅዱስ ይመሰክራል፡፡ ያንጊዜ ሕዝቡ ሁሉ ተማርከው ፋርስ ባቢሎን ሲወርዱ፤ በሕዝቡ ሁሉ ላይ ናቡከደነፆር ሲሠለጥንባቸው እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ለአሕዛብ ከመገዛት ጠበቃት፤ የጽዮንን ልጆች ያገኛቸው መከራ በኢትዮጵያ ላይ አልደረሰባትም፤ ነቢዩ ኤርምያስ የመከራው ቀን እየደረሰ እየደረሰ ሲመጣ ሞትም በእስራኤል ፊት ጥላውን ሲያጠላ የኢትዮጵያ ነገር እጅግ አሳስቦታል  ‹‹ይህን ኢትዮጵያዊ ምን ላድርገው›› ብሎ እግዚአብሔርን ጠየቀ እግዚአብሔርም ለድውያን የሚሆነውን ፈውስ ቆርጦ በሙዳዩ ይዞ እንዲመጣ እዘዘው አለው፤ ኢትዮጵያዊው ሰው እንደታዘዘ ቆርጦ በሙዳይ የጨመረውን መድኃኒት ይዞ ሲመለስ ከመከራ ለመዳን የተዘጋጀለትን እንቅልፍ ለስድሳ ስድስት ዘመናት አንቀላፋ፡፡
ይህ የፈውስ ዛፍ ሕሙማን የተፈወሱበት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ነው፤ ኢትዮጵያዊው ሰው ከሕሙማኑ ሳያደርሰው ለላከው ነቢይ ለኤርምያስም ሳይሰጠው መቅረቱ ለምን ይመስልሃል? ዘመኑ ገና መሆኑን ያጠይቃል፡፡ ነገር ግን ቢያንቀላፋም በእጁ ያለውን የፈውስ እንጨት በዓለም ያሉ ሕሙማን ሁሉ በተስፋ የሚጠብቁት ስለሆነ አልጣለውም፤ ስልሳ ስድስት ዘመን ሙሉ ቅጠሉ ሳይጠወልግ ደሙ ሳይደርቅ መኖር እንዴት ያለ ድንቅ ነገር ነው?!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን በዚያ የመከራ ዘመን ለእስራኤል ሁሉ የተዘጋጀውን መድኃኒት በእጇ ላይ ሲያስቀምጥላት ኢትዮጵያም ቅጠሉ እንዳይጠወልግ ደሙም እንዳይነጥፍ አድርጋ በሙዳይ ውስጥ ስታስቀምጥ ስንመለከት ኢትዮጵያ ለእግዚአብሔር የታመነች ሀገር እንደሆነች ያመላክታል፡፡ መድኃኒቱን ከእስራኤል እጅ አውጥቶ በኢትዮጵያ እጅ ማኖሩ ኢትዮጵያ ለእግዚአብሔር ሥራ የተመቸች ሀገር ስለሆነች ነው እንጅ ሌላ ምንድነው?
በሐዲስ ኪዳን የፈውስ ዛፍ መስቀል ነው፤ በቀደመው ዘመን ኢትዮጵያዊው ሰው አቤሜሌክ በሙዳዩ ያስቀመጠው ከእስራኤላውያን እጅ የወጣው በኢትዮጵያውያን እጅ የገባው የፈውስ እንጨት ቅዱስ መስቀል ነው፡፡ ዛሬ በታሪከ ኢትዮጵያ ታላቁን የመስቀልን በዓል እያከበርን ያለነው እንደ ሌሎቹ ሀገራት በክርስቶስ መስቀል አምሳል የተሠሩ መስቀላትን ይዘን አይደለም እራሱን የክርስቶስን መስቀል ይዛ ኢትዮጵያ መስቀሉን ታከብራለች፡፡ እንደ እመቤታችን ማርያም፣ እንደ ማርያም መግደላዊት ከመስቀሉ እግር ሥር ቆማ ኢትዮጵያ ስለመስቀሉ ‹‹ዮም መስቀል ተሰብሐ›› እያለች በያሬዳዊ ዜማ ትዘምራለች፡፡
ዓለም ቢያምንም ባያምንም ዛሬም ዓለም የሚድንበት የፈውስ እንጨት ያለው በኢትዮጵያ እጅ ነው፡፡ ወደ ቀድሞው ታሪክ ስንመለስ ሕዝቡ ወዲያውኑ መድኃኒቱን ሊቆርጥ የተላከው  ኢትዮጵያዊው ሰው ሳይመለስ በዚያች ክፉ ሌሊት ሕዝቡ ተማከው ፋርስ ባቢሎን ገብተው ስላደሩ ሳይጠቀሙበት ቀሩ፤ ዛሬም ዓለም በሰይጣን ተማርኮ ስለተወሰደ እግዚአብሔር ባዘጋጀለት መድኃኒት በቅዱስ መስቀል ባይጠቀምበትም ኢትዮጵያ ግን በልቧ ይዛው ትኖራለች፡፡
የኢትዮጵያ ልጆች ስሙኝ!  በኋላም ቢሆን የማታ ማታ ለመላው ዓለም የመዳን ዐዋጅ የሚታወጀው ከዚህች ሀገር ነው ፡፡ ለእስራኤል ከሰባ ዓመት የስደት ቆይታ በኋላ የመመለሳቸው ዜና የተነገረው በኢትዮጵያዊው ሰው በአቤሜሌክ በኩል ነው፡፡ አሁንም ላለው ትውልድ እግዚአብሔር ከሰይጣን አገዛዝ ነጻ የሚወጣበትን ዐዋጅ የሚያውጀው በኢትዮጵያ በኩል ነው፡፡ ሁልጊዜ ትኩስ የሆነው የጌታ ደም የሚፈስበት ፈውስ የማይነጥፍበት ቅዱስ መስቀል በእጇ ነውና፡፡
በእርግጥ ስለ መስቀል ስናሣ ኢትዮጵያ ከዚህም የሚቀድም ታሪክ አላት፡- ንግሥተ ሳባ ወደ ሰሎሞን በሄደች ጊዜ ከሰሎሞን ቤተ መንግሥት ወድቆ ያገኘቸው ግንድ እግሯ ላይ የወጣባትን ነውሯን እንዳስወገደላት እናውቃለን፡፡ ይህ ግንድ ባደረገው ተዓምራት የተነሣ እሷም እሱም አዋጥተው በብር ለብጠውታል፡፡ ከሰሎሞን በኋላ የተነሡ ነገሥታትም ይህን ግንድ በብር ይለብጡት ነበር፤ በቁጥር 28 የሚሆኑ ነገሥታት ከሰሎሞን በኋላ ነግሠዋል ከንግሥተ ሳባ እና ከሰሎሞን ጋር ሠላሳ ይሆናሉ፤ አይሁድ ጌታን የሚሰቅሉበት ጊዜ ሲደርስ ለይሁዳ የሰጡት ሠላሳ ብር የተገኘው ነገሥታቱ ለዚህ ግንድ ሲለብጡት ከኖሩት ነው፡፡
ብሩን ለይሁዳ ሰጥተው በግንዱ ጌታን ሰቀሉበት፤ ስለዚህ በመስቀሉ ከዓለም ቀድመን የተፈወስን እኛ መሆናችንን ተመልከቱ፤ ንግሥተ ሳባ የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን ትወክላለች እና፡፡ መስቀሉን በማክበርስ ከእኛ ከኢትዮጵያውያነ የሚቀድም ማነው? እኛ አይደለንም እንዴ ከሰሎሞን ቀድመን በብር ያስጌጥነው? መንፈስ ቅዱስ ኢትዮጵያን ጥንትም ቢሆን ሥራ እንደሚያሠራት ተመለክቱ የእግዚአብሔር ጥበብ ነው እንጅ በእውነት ለግንድ ብር አውጥቶ የሚሸልም ማነው? ይህ በሰሎሞን ቤተ መመንግሥት በር ላይ የወደቀው ግንድ እንዲሁ እንደሌሎች ግንዶች አይደለም ይህን መንፈስ ቅዱስ ከገለጠላት ኢትዮጵያ በቀር ሌላ ማን ሊያውቅ ይችላል?
ዛሬስ ቢሆን መስቀሉን ኢትዮጵያ ስታከብረው መስቀሉን ከሌላው እንጨት መለየት አቅቷቸው እንደ ግብዝ የሚመለከቷት ሳይኖሩ ይቀራሉ ብላችሁ ነው? አባቶቻን ግን መንፈስ ቅዱስ ያለበማቸው ስለነበሩ ግብጻውያንን ዓባይን እንገድብባችኋለን ብለው በማንገራገር እጅ መንሻ እንስጣችሁ ሲሏቸው ከመስቀሉ በቀር ሌላ የሚያጠግባቸው እጅ መንሻ ቢያጡ መስቀሉን እጅ መንሻ አድርገው ተቀበሏቸው፤ ግብጽ አሳልፋ በረከቷን ለኢትዮጵያ ሰጠች፡፡ በእርግጥ ግብጽ ቀደም ሲል እንደነገርኋችሁ ስለመስቀሉ የኢትዮጵያን ያህከል ደጅ ጥናት አላደረገችም ኢትዮጵያ በንግሥተ ሳባ በኩል ለመስቀሉ እጅ መንሻ አቅርባለች፣ በአቤሜሌክ በኩል ስልሳ ስድስት ዘመን ሙሉ ስለ መስቀሉ ከሀገር ወጥታ ተሰዳለች፡፡ ስለዚህም አግዚአብሔር እውነተኛ ፍርድ ፈረደ፤ ደጅ የጠናችው ኢትዮጵያ በዐፄ ዳዊት ምክንያት መስቀሉን ተቀበለች፡፡
እሳቸውም መስቀሉ ስናር ላይ ሲደርስ መስቀሉን ሊቀበሉ ከመናገሻ ከተማቸው እንደወጡ ሳይመለሱ ቀሩ ሞት ወስዷቸዋልና፡፡ ልጃቸው ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ መንበረ መንግሥታቸውን ሲረከቡ አባታቸው ዐፄ ዳዊት የጀመሩትንም ሥራ አብረው ተረከቡ፤ መስቀሉን ወደ ኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ አመጡ በመናገሻ ከተማቸው በደብረ ብርሃን ከቤተ መንግሥታቸው ጎን ሊያኖሩት ተመኙ ልብ ላለው ሰው ከመስቀሉ አጠገብ መራቅ እንዴት ይከብዳል!? እመቤታችን፣ ጌታ የሚወደው ደቀ መዝሙር ዮሐንስ እናሌሎችም ቅዱሳን ያሉት በዚያ ነውና፡፡  እግዚአብሔር ግን አስቀድሞ ወዳዘጋጀው ሥፍራ ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ እንዲወስዱት በራዕይ አዘዛቸው፡፡ መስከረም አሥር ቀን ወደ ኢትዮጵያ የገባውን መስቀል መስከረም ሃያ አንድ ቀን በግሼን መስቀለኛ አምባ ላይ አስቀመጡት፡፡
ኢትዮጵያ መስቀላዊት ሀገር መስቀለኛ ተራራ የሚገኝባት ምድር፡፡    

No comments: