>

Wednesday, 18 September 2019


የነፍሴ ጥያቄ
ያለ ጥያቄ በተፈጠረ ዓለም ውስጥ በጥያቄ የተሞላ ሕይወት ያለን የሆንነው ለምንድነው? ሳንጠይቅ ተፈጥረን ያለጥያቄ መሻታችን የማይፈጸምልን ለምንድነው? በውኑ ለምኖ ሰው የሆነ ከእኛ መካከል አለ? አጭር፣ ረጅም፣ ቀይ፣ ጥቁር ለመሆን ሀሳብ ያቀረበ ማነው? ማንም! አደል እንዴ!? ተሳሳትሁ?
ታዲያ ሳንለምን በተፈጠረ ሰውነታችን ውስጥ ጥያቄ ያለባት ነፍስ እንዴት ተገኘች? ነፍሳችን በራሷ ሳንለምነው እግዚአብሔር ከባሕርዩ ቸር መሆን የተነሣ ሕያዋን ይሁኑ ብሎ የሰጠን ስጦታ አይደለችምን? ዘፍ 2፥7 እስትንፋሱን ሳንለመነው የሰጠን አምላክ መልክዓ መለኮቱን ‹‹ሰውን በመልካችን በምሳሌአችን እንፍጠር›› ብሎ በገዛ ፈቃዱ መለኮቱን ይመስል ዘንድ ለፈቀደለት ሰው ‹‹ለምኑ ይሰጣችኋል›› ሉቃ 11፥9፣ ዮሐ 14፥13፣ 15፥7 ብሎ ማስተማር ተገቢ ነው? ሳንለምነው ፈጥሮ እንዴት ለምኑ ይለናል?
እንዲያውም ቅዱስ ያዕቆብ ‹‹ትመኛላችሁ አታገኙም በብርቱ ትፈልጋላችሁ ልታገኙ አትችሉም ትጣላላችሁ ትዋጉማላችሁ ነገር ግን አትለምኑምና ለእናንተ አይሆንም›› ያዕ 4፥2 ማለቱ ያለ ልመና የምናሳካው ምንም ነገር የለም ማለቱ ነው? እግዚአብሔር የምሻውን የልቤን ጉዳይ ያውቀው የለ እንዴ? ለምንድነው እንደ ምድር ባለጠጎች እንድለምነው የሚያበረታታኝ ? ሳልለምነው ቢያደርግልኝ ምን ነበረበት? ጸሎትም ሲያስተምረኝ ልመና የተሞላበት ጸሎት አስተማረኝ፤ ‹‹የዕለት እንጀራችንን ስጠን ዛሬ በደላችንን ይቅር በለን…ወደ ፈተና አታግባን ከክፉ ሁሉ አድነን ›› የሚል ልመና የሚበዛበት ጸሎት አለኝ ይሄ አግባብ ነውን?
በእርግጥ ጥያቄ ሁሉ ልመና አይደለም፤ እኔን ያስገረመኝ መቼ ነው ያለ ጥያቄ መኖር የሚቻለው? ከዚህ ደረጃ ላይ የደረሰስ ማነው? የምታውቁት ሰው አለ? ጥያቄዎቹ ሁሉ ተመልሰውለት በኅሊና ፀጥታ ውስጥ እየኖረ ያለ ሰው አለ? የሚለው ነው፡፡
የተወደዳችሁ የልዑል አምላክ የእግዚአብሔር ቤተ ሰቦች! እኔ በዚህ ርዕስ ውስጥ ማንሣት የፈለግሁት ያለ ጥያቄ ተፈጥረን ጉዟችንን እስከምናጠናቅቅ ድረስ በጥያቄ የተሞላ ኑሮ ይገጥመናል ጥያቄው አንዳንዱ የሚመለስ ሌላው ደግሞ የማይመለስ ሊሆን ይችላል ይህ ለምን ሆነ? ጠያቂ መሆናችንስ ጉዳት ይኖረው ይሆን? በነገራችን ላይ ይህ በሰው እና በመላእክት ሕይወት ውስጥ የሚታይ እንጅ ለሌላው ፍጥረት የለውምና ለእኛ ይህ መሰጠቱ ጉዳት ካለው እድንወያይበት ብየ ነው፡፡
ለጊዜው የነፍሴ ጥያቄ ያልኳቸው በኔ ውስጥ የሚመላለሱትን ነው በእናተም ውስጥ ያሉትን ንገሩኝ ቅዱሳን አበው፣ ቅዱሳት መጻሕፍት፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሰው ልጆች ጥያቄ የመለሰችውን መልስ እነግራችኋለሁ፡፡ 
 በዚህ ገጽ አስተያየት ለመስጠት ስለሚያስቸግር እኔም ለማየት ስለሚያስቸግረኝ simakone2006@gmail.com ብላችሁ መልዕክት ብታስቀምጡልኝ ደስ ይለኛል፡፡
    ?

1 comment:

Unknown said...

ቅዱሳን ያማልዳሉ ሲባል፦ በአካለ ስጋ እያሉ እነሙሴ ድንግል ማርያም በሰርጉ ቤት ምልጃን አቅርበዋል ።እኒህ በአካለ ስጋ እያሉ ነው።እኛስ አማልዱኝ ብለን የምንጠይቀው በአካለ ነፍስ ላሉት ቅዱሳን ነው ወይስ በአካለ ነፍስ ላሉቱ?

0941110203